Tuesday, March 15, 2016

በትላንትናው ምሽት የቱርኳ ዋና ከተማ አንካራ በፍንዳታ ተናጠች


በትላንትናው እለት ምሽት በቱርክ አንካራ በተከሰተ ፍንዳታ የ37 ሰዎች ህይዎት ሲቀጠፍ ከመቶ በላይ ከባድ እና ቀላል የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል። ይህ አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በከተማዋ ዕምብርት ላይ የደረሰ ሁለተኛው ጥቃት ነው ተብሏል። በመኪና ላይ የተቀነባበረው ፍንዳታ ከኩርድ አማጽያን (ነጻ አውጭ) ቡድን ጋር ግንኙነት ባላት ሴት እንደተፈጸመ ታውቋል። ባለፈው ወር የካቲት 9 / 2008 በተመሳሳይ መልኩ 28 ሰዎች ሲገደሉ 61 ያህል መቁሰላቸው የሚታወስ ነው። ሁለቱም ፍንዳታዎች የተፈጸሙት የበርካታ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች መገኛ እና የከተማው ማዕከል በሆነው ”ክዝላይ” በተሰኘው ቦታ ላይ መሆኑ ተዘግቧል። ቀዳሚው ፍንዳታ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ መስሪያ ቤት አጠገብ የተፈጸመ ሲሆን ፤ በወቅቱ ከስራ የውጡ ወታደሮች እና ሲቪል ዜጎችን ያሳፈሩ የሰራተኛ ማጓጓዣ አውቶቡሶች ላይ ያነጣጠረ ነበር።
የትላንትናው ፍንዳታ ደግሞ የከተማ ውስጥ የህዝብ ማመላለሻ አውቶብሶች መነሻ አቅራቢያ አሸባሪዋ የራሷን መኪና በተጠመደ ቦንብ በማፈንዳቷ መድረሱ ነው የታወቀው። ተሳፋሪ ጭኖ ለጉዞ ይንቀሳቀስ የነበረ አንድ አውቶቡስና ሌሎች በዙሪያው ያሉ በርካታ አውቶሞቢሎች ተቃጥለዋል። በጥቃቱ ሰለባ የሆኑት በሙሉ ሰላማዊ ዜጎች መሆናቸው ታውቋል። በተለይም በትላንትናው ዕለት በሀገሪቱ ሙሉ የተከናወነውን የከፍተኛ ትምህርት መግቢያ ፈተና አጠናቀው ለመዝናናት ወደቦታው የወጡ ወጣቶችና ቤተሰቦቻቸው የጉዳቱ ተጠቂ እንደነበሩ የዜና ምንጮች ጠቁመዋል።
ፍንዳታውን ተከትሎ የቱርኩ ፕሬዝዳንት ረጀብ ጠይብ ኢርዶጋን በሰጡት መግለጫ ”መንግስታችን ለሚሰነዘርበት ማንኛውም የሽብር ጥቃት ፣ ራስን የመከላከል ህጋዊ መብቱን ተጠቅሞ ፣ ተገቢውን ምላሽ ከመስጠት ወደኋላ አይልም” ካሉ በኋላ ህዝቡ ከየትኛውም ጊዜ በበለጠ ባንድነት እንዲቆም ጥሪያቸውን ማስተላለፋቸው ታውቋል።
በመግለጫቸው ”ቱርክ በመካከለኛው ምስራቅ ቀጠና በተፈጠረው ያለመረጋጋት ምክንያት የሽብር ኢላማ እየሆነች ነው” ያሉ ሲሆን ፤ አስከትለውም ”የሽብር ቡድኖች እና እነሱን በሽፋንነት የሚጠቀሙ ኃይሎች ከጸጥታ ኃይሎቻችን ጋር በሚያደርጉት ትንቅንቅ ሽንፈትን ሲከናነቡ ፤ እጅግ አሳፋሪና ከስነ ምግባር ባፈነገጠ መልኩ ሲቪል ዜጎቻችን ለማጥቃት የትኛውንም አማራጭ መከተልን መርጠዋል” ሲሉ ተደምጠዋል። ያገራችን ሉዓላዊነት እንዲሁም የህዝባችንን አንድነት ዒላማ ያደረገው ይህን መሰል አጸያፊ ጥቃት በሽብር ትግሉ ላይ ያለንን ቁርጠኝነት ፈጽሞ አይቀንሰውም፤ ይልቁንም ጽናትን ያላብሰዋል ሲሉ አክለዋል ፕሬዝዳንቱ።
የቱርኩ ፕሬዝደንት በፍንዳታው ምክንያት ወደ አዘርባጃን ዋና ከተማ ባኩ ለመሄድ የነበራቸውን ዕቅድ መሰረዛቸው የታወቀ ሲሆን በሌላ በኩል ግን የሁለትዮሽ ስብሰባው ወደ ቱርክ ዙሮ በነገው ዕለት በአንካራ ከተማ ሊካሄድ መሆኑ ተዘግቧል። ይህ ስብሰባ ከወር በፊት ታቅዶ የነበረ ወሳኝ የትብብር ውሎች የሚፈረሙበት ሲሆን ባለፈው ወር በደረሰው ጥቃት ምክንያት የተራዘመ ነበር። ይህን ተከትሎም የአዘርባጃን ፕሬዝደንት ኢልሃም አሊየቭ ወደ ቱርክ ለመምጣት መወሰናቸው ለቱርክ ያላቸውን ድጋፍ እና ጥብቅ ጉድኝት ማሳያ ተደርጎ የሚታይ ነው። ለአምስተኛ ጊዜ በሚከናወነው በዚህ ከፍተኛ ስትራቴጂያዊ የትብብር ካውንስል ለሁለቱ ሀገራት ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ወሳኝ ስምምነቶች ይፈረማሉ ተብሎ ይጠበቃል።

No comments:

Post a Comment