Friday, March 11, 2016

ጥቂት ነጥቦች “ይቅርታ” ስለተባለው ጉዳይ ከዶ/ር ታደሰ ብሩ


በኢህአዴግ ድረ ገጽ የወጣው ነው ተበሎ በማኅበራዊ ሚዲያ ሲዘዋወር ያገኘሁት ባለ አንድ ገጽ አንቀጽ መግለጫ አይሉት ዜና አዟዙሬ ብመለከት ትርጉሙ አልገባ ብሎኛል። የመግለጫ/ዜናው ሙሉ ቃል የሚከተለው ነው።
=========
ለተፈጠረው ችግር የፌደራል መንግስት ይቅርታ ይጠይቃል!!
በኦሮሚያና አንዳንድ የአማራ አካባቢዎች የተከሰተው ችግር ሌላ ምክንያት ሳናበዛ ህዝቡ ከፍተኛ ምሬት ስላለውና በአገልግሎት አሰጣጥ እየተፈጠረ ባለው ከፍተኛ ቅሬታ ዝም ብሎ ለመቀበል ዝግጁ ያልሆነ ወጣት ትውልድ በመፈጠሩ ነው። እናም ከሰሞኑ በተፈጠረው ችግር የፌደራል መንግስት ይቅርታ ይጠይቃል።
=========
በዚህ አንቀጽ ውስጥ ያሉት አሻሚ ነገሮች ብዙ ናቸው፤ ዋና ዋናዎቹን ልዘርዝር
1. ይህ ጽሁፍ “ከሰሞኑ በተፈጠረው ችግር” የፌደራል መንግሥት ይቅርታ መጠየቁን የሚገልጽ መግለጫ ነው ወይስ የፌደራል መንግሥት ከሰሞኑ (ማለትም በሚቀጥሉት ቀናት) ይቅርታ የሚጠይቅ መሆኑ የሚገልጽ ዜና ነው?
2. በመግለጫው መሠረት የችግሩ ምክንያቶች ሶስት ናቸው፤ እነሱም
2.1. ሕዝቡ ከፍተኛ ምሬት ያለው መሆኑ፣
2.2. በአገልግሎት አሰጣጥ እየተፈጠረ ባለው ከፍተኛ ቅሬታ፣ እና
2.3. ይህንን ቅሬታ ለመቀበል ዝግጁ ያልሆነ ወጣት ትውልድ መፈጠሩ።
ተራ ቁጥር 2.1 እና 2. 2 ተመሳሳይ መልዕክት ነው የሚደግሙት። በመሰረቱ መግለጫው ማትኮር የነበረበት በምሬትና ቅሬታዎቹ ምክንያትሊሆን ይገባ ነበር፤ ለጊዜው እንተወው።
ተራቁጥር 2.3. አሻሚም፣ አስገራሚም ገራሚም ነው። በአንድ በኩል የችግሩ ምክንያት “ቅሬታ ለመቀበል ዝግጁ ያልሆነ ወጣት ትውልድ መፈጠሩ” መሆኑን በመግለጽ እንዲህ ዓይነት ትውልድ መኖሩ አደጋ እንደሆነ አድርጎ ያቀርበዋል። በሌላ በኩል ደግሞ ችግሩ ራሱ የተቀሰቀሰው ኢህአዴግ “ቅሬታ ለመቀበል ዝግጁ ያልሆነ ወጣት ትውልድ” በመፈጠሩ እንደሆነ በዚህም ምክንያት ችግሩ ራሱ የልማት (የሰዋዊ ልማት) ውጤት እንደሆነ ያቀርበዋል። የመግለጫው አርቃቂዎች ሁለተኛውን አስበው የፃፉት ይመስለኛል፤ ይህ ትክክል ከሆነ የሚቀጥለውን ጥያቄ ያስነሳል።
3. ለመሆኑ ከ500 በላይ ዜጎች የተገደሉት በአስር ሺዎች የታሰሩትና የተደበደቡት “ቅሬታ ለመቀበል ዝግጁ ያልሆነ ወጣት ትውልድ” መፈጠር አለመፈጠሩን ለማረጋገጥ ነበርን? እንዲህ ዓይነቱ ወጣት የተፈጠረው “በኦሮሚያና አንዳንድ የአማራ አካባቢዎች” ብቻ ለምን ሆነ፤ ሌሎቹ በሰዋዊ ልማት ወደኋላ ስለቀሩ ነው?
4. የፌደራል መንግሥት ይቅርታ የጠየቀው (ሀ) ችግር የተባለው ነገር ስለተፈጠረ ነው? (ለ)ቅሬታ ለመቀበል ዝግጁ ያልሆነ ወጣት ትውልድ በመፈጠሩ ነው? ወይስ (ሐ) በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በግፍ በመገደላቸው፤ በአስር ሺዎች የሚገመቱ ዜጎች በመደብደባቸውና በመታሰራቸው ነው? መግለጫው ግልጽ አይደለም።
የፌደራል መንግሥት ይቅርታ የጠየቀው (ወይም ሊጠይቅ ያሰበው) በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በግፍ በመገደላቸው፤ በአስር ሺዎች የሚገመቱ ዜጎች በመደብደባቸውና በመታሰራቸው ከሆነ መግለጫው በጎ ጅምር ተደርጎ ሊወሰድ ይገባል። ይሁን እንጂ ይቅርታ በብዙ ኩነቶች የታጀበ ሂደት እንጂ በአንዲት አደናጋሪ መግለጫ የሚጠናቀቅ ነገር አይደለም። ይቅርታው የምር ከሆነ
1. በምን ምክንያት ይቅርታ እንደተጠየቀ ግልጽ ይደረግ፤
2. ለምክንያቶቹ ዘላቂ መፍትሄ የሚሰጥበት መንገድ ይዘጋጅ፤
3. እየገደሉ ይቅርታ የለምና ከሁሉ አስቀድሞ ግድያው፣ እስርና ድብደባው ይቁም፤
4. የታሰሩት ይፈቱ፤ በይፋ ይቅርታ ይጠየቁ፤ ለደረሰባቸው ጉዳት ካሳ ይከፈላቸው፤
5. ሕይወታቸውን ያጡ ወገኖች የሰማዕትነት ክብር ይሰጣቸው፤ ቤተሰቦቻቸውም ካሳ ይከፈላቸው፤
6. በዚህ “ችግር” ሰበብ የገደሉ፣ ያስገደሉ፤ የደበደቡ፣ ያስደበደቡ፤ ያሰሩ፣ ያሳሰሩ ተገቢውን ቅጣት ያግኙ፤
7. ወደፊት ተመሳሳይ ነገር እንደማይደገም ማረጋገጫ ይሰጥ፤ እና
8. ሕዝቡ “ቅሬታ ለመቀበል ዝግጁ ያልሆነ ወጣት ትውልድ” በመፈጠሩ የተሰማውን ደስታ በይፋ እንዲገልጽ ሁኔታው ይመቻች፤ ይህ ወጣት ሌላም ቅሬታ ካለው እንዲገልጽ ይበረታታ።

No comments:

Post a Comment