Friday, August 28, 2015

የቀድሞ አንድነት ፓርቲ ማህበራዊ ጉዳዮች ኃላፊ አቶ አለነ ማህፀንቱ ውሳኔ ሳያገኙ ቀሩ


‹‹ስብስባን በማወክ›› ወንጀል የተከሰሱት የቀድሞ አንድነት ፓርቲ ማህበራዊ ጉዳዮች ኃላፊ አቶ አለነ ማህፀንቱ ውሳኔ ሳያገኙ ተለዋጭ ቀጠሮ እንደተሰጣቸው፤ የተከሳሹ ጠበቃ አቶ ገበየሁ ይርዳው ገለፁ፡፡
አቶ አለነ ዛሬ ነሐሴ 21 ቀን 2007 ዓ.ም አራዳ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ቀርበው የነበረ ሲሆን፤ መዝገባቸውን እየተከታተለ የሚገኘው ተረኛ ችሎትም መዝገቡን እየተመለከተ እንዳለና ብይኑ እንዳልደረሰ ገልፆ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ አቶ ገበየሁ፣ የፍርድ ቤቱን ውሳኔ እንደተቃወሙና ደምበኛቸው ብይን ለማግኘት ይህን ያህል ጊዜ መንገላታት እንደሌለባቸው እንዲሁም ዋስትናቸውን መከልከላቸው አግባብ እንዳልሆነ ለተረኛው ችሎት አስረድተዋል፡፡ ተረኛ ችሎቱ ብይኑ ስላልደረሰ ውሳኔ ላይ እንዳልደረሱ በመግለፅ ውሳኔውን ለማስተላለፍ ማለትም አቶ አለነ ‹‹ክሳቸውን ሊከላከሉ ይገባል ወይስ መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ ተሰናብተዋል›› በሚለው ላይ ብይኑን ለማስተላለፍ ተለዋጭ ቀጠሮ ለመስከረም 5 ቀን 2008 ዓ.ም ሰጥቷል፡፡
አቃቤ ህግ በአቶ አለነ ማህፀንቱ ላይ ሁለት ምስክሮችን አሰምቶ ተከሳሹ ብይን ሳያገኙ፤ መዝገባቸው ከመደበኛ ችሎት ወደ ተረኛ ችሎት እንደተላለፈ ይታወቃል፡፡ አቶ አለነ መንግስት አይኤስን ለማውገዝ በጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ‹‹ስብሰባን አውከዋል›› የሚል ክስ ቀርቦባቸው፤ ክሳቸውን ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት በመሆን ከግንቦት ወር 2007 ዓ.ም ጀምሮ እየተከታተሉ እንዳለ አይዘነጋም፡፡

No comments:

Post a Comment