Tuesday, January 26, 2016

የከሸፈው ዲፕሎማሲያችን፤ ከጠረፍ እስከ ከተማው!


በሳውዲ የመን የሚገኙ የሳውዲ ከተሞችን በስራ ጉዳይ ተዘዋውሮ የማየት እድል አጋጥሞኛል ። በተዘዋወርኩባቸው አጋጣሚዎች ቁጥራቸው በርከት ያሉ በህገ ወጥ ድንበር ሰብረው የገቡና በህጋዊው መንገድ ወደ ሳውዲ ገብተው በዚያው የከተሙ ቁጥራቸው ከፍ ያለ ኢትዮጵያውያን ወገኖቸን አግኝቼ ሳውዲ ስላደረሳቸው መንገድ ብዙ አውግተናል ። በተለይ በሕገ ወጡ የየመን ድንበር መጥተው በእረኝነትና በጉልበት ስራ ተሰማርተው የሚሰሩ ወንድሞቸን አግኝቼ በየመን ድንበር ሽግግር ስለሚያጋጥማቸው ክልትም ፣ በድለላ ስራ ላይ በናጠጡ የራሳችን ዜጎች ከአረብ አሸጋጋሪዎች ጀምሮ እስከ ከተማ ህግ አስጠባቂ ነን ባዮች ደርሶባችው ያሳለፉትን ሰቆቃ የተጎዳ ብልት ገላቸውን ሳይቀር እያሳዩ ሲናገሩት አድምጫለሁ ።
በየመን ድንበር ከባቢ በአሸጋጋሪዎች ከሚሰሩት ያልተነገሩ ወንጀሎች ተጠቂዎች የተሻለ ኑሮ ፍለጋ በሉት ከድህነት ፣ ኑሮ ውድነት ሸሽተው ወደ ሳውዲ የሚመጡት እህቶች ይገኙበታል ። በሴቶች ላይ የሚፈጸመው ግፍ ደግሞ በአይነቱ ለየት ያለና ሰቅጣጭ ነው ። እኒህ መከረኛ ኢትዮጵያውያት ተበድረውና ተቀድመው የየመን ሳውዲን ድንበር ለመሻገር ሲሞክሩ የአደንዛዥ እጽ ነጋዴዎች ማሸጋገሪያነት ኢላማ የወደቁ አውቃለሁ ። ጥቂት የማይባሉት እኒህ ወገኖች በወንጀል ተከሰውና ተፈርዶባቸው ለአመታት ኑሯቸውን በሳውዲ እስር ቤት ማድረጋቸው በገሃድ የማይበገር የ ኢትዮጵያውያን በሳውዲ ያልተነገረ ህይዎት ነው ። ይህ መሰሉን እውነት የምናገረው ከጉዳዩ ባለቤት ተገፊዎች ተደጋግሞ የምሰማው አቤቱታ ነው ። ድንበሩ ቀርቶ በመሐል ከተማው ፣ የመብት ገፈፋ የደረሰባቸውን ዜጎች በቆንስልና ኤምባሲው በር ላይ መጥተው ሲወድቁ በአግባቡ አይስተናገዱም ። … በየጉራንጉሩ በዜጎች ላይ ለሚደርሰው በደል ጠያቂ አጥተናል ። ጀሯችን ለማድመጥ አይናችን ለማየት ፤ እግራችን ለመሄድ ከቻለ እዚህም እዚያም በርካታ ልንናገረው የሚከብደውን መረጃ እንሰማለን ፤ እናያለን !ግን ለማን አቤት ይባላል ?… በምዕራብ ሳውዲ የተለያዩ እስር ቤቶች የሚገኙ ከ350 በላይ ከሚገመቱት እስረኞ መካከል የተወሰኑትን በተደጋጋሚ አግኝቻቸው የመንግስት ተወካዮቻችን ለአመታት በእስር ሲማቅቁ አንድም ቀን ጎብኝተዋቸው እንደማያውቁ አጫውተውኛል እንባ እያዘሩ አጫውተውኝ ያውቃሉ…
ያገባኛል ፣ ያስተምራልና ስለማውቀው የስደተኛ ህይዎት እውነተኛ ገጽታ አመሰክራለሁ ! የቀለም ቀንድ ጋዜጣ ዘወትር ማክሰኞ በሐገር ቤት የሚታተም ጋዜጣ ነው ። በዛሬው እትሙ የእኔን ማስታወሻና ሌሎች ዳጎስ ደጎስ ያሉ መረጃዎችን ይዟል ! ” ያነበበ ተጠቀም ” የቀለም ቀንድን ያንብቡ !
መልካም ቀን !
ነቢዩ ሲራክ

No comments:

Post a Comment