Thursday, February 4, 2016

እነ ብርሃኑ ተ/ያሬድ በፍርድ ቤት እየተጉላሉ መሆኑን አቤቱታ አሰማ *ተከሳሾች ችሎቱ እንዲቀየርላቸው ጠይቀዋል


12654365_1033159216731083_8629514336522688637_nበፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ ቀርቦባቸው ጉዳያቸው በከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት እየታየ የሚገኙት እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ በፍርድ ቤት እየተጉላሉ መሆናቸውን በመግለጽ ችሎት እንዲቀየርላቸው አቤቱታ አቅርበዋል፡፡
ዛሬ ጥር 26/2008 ዓ.ም ልደታ ፍርድ ቤት የቀረቡት ተከሳሾች አቶ ብርሃኑ ተ/ያሬድ፣ ወ/ት እየሩሳሌም ተስፋው፣ አቶ ፍቅረማርያም አስማማው እና አቶ ደሴ ካህሳይ ጉዳያቸውን እያየ የሚገኘው 14ኛ ወንጀል ችሎት ጉዳያቸውን በማጓተት እያጉላላቸው እንደሆነ በአቤቱታቸው ገልጸዋል፡፡ መዝገቡ ለዛሬ ተቀጥሮ የነበረው ለብይን ቢሆንም ተከሳሾች 14ኛ ወንጀል ችሎት እንዲቀየርላቸው አቤቱታ በማሰማታቸው ብይኑ ሳይሰማ ቀርቷል፡፡
1ኛ ተከሳሽ ብርሃኑ ተ/ያሬድ ‹‹አቃቤ ህግ አንድ ምስክሩን ያሰማው ነሐሴ 12/2007 ዓ.ም ነው፡፡ የአንድ ምስክር ቃል በጽሁፍ ተገልብጦና ተመርምሮ ብይን ለመስራት ይህን ያህል ጊዜ መውሰድ አልነበረበትም፡፡ ለዚህ ሁሉ መጉላላት ይህ ችሎት አስተዋጽኦ አለው ብለን ስለምናምን ችሎቱ እንዲቀየርልን ለፍርድ ቤቱ ፕሬዚዳንት ቢሮ አቤት ብለናል፡፡ ስለዚህ ብይኑ ዛሬ ሊሰማብን አይገባም›› ብሏል፡፡
3ኛ ተከሳሽ ፍቅረማርያም አስማማው በበኩሉ ‹‹ችሎቱ ለአቃቤ ህግ ወገንተኝነት ያሳያል ብለን ስለምናምን ችሎቱ እንዲቀየርልን የጠየቅነው አቤቱታ ላይ ብይን ሳይሰጥ ጉዳያችንን ችሎቱ እንዳያይ ይደረግልን›› ሲል ተናግሯል፡፡ ችሎቱ አቤቱታው ለምን ለፕሬዝዳንቱ እንደቀረበ ግልጽ እንዳልሆነለት በመግለጽ አቤቱታው ለራሱ ለችሎቱም እንዲደርሰው ጠይቆ ከተከሳሾች እንዲደርሰው አድርጓል፡፡
በሌላ በኩል 4ኛ ተከሳሽ አቶ ደሴ ካህሳይ የትግርኛ ቋንቋ ተናጋሪ መሆናቸው ታውቆ አስተርጓሚ እንዲመደብላቸው ጠይቀው እንደነበር በመግለጽ እስካሁን አስተርጓሚ እንዳልተመደበላቸው ገልጸዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ ተከሳሾች ባቀረቡት አቤቱታ ላይ ብይን ለመስጠት በሚል ለየካቲት 4/2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
እነ ብርሃኑ ተ/ያሬድ በተወካዮች ምክር ቤት በአሸባሪነት የተፈረጀውን ግንቦት ሰባት የተባለ የፖለቲካ ድርጅት ለመቀላቀል ወደ ኤርትራ ሲያመሩ ማይካድራ የተባለ የድንበር ከተማ ላይ መያዛቸውን አቃቤ ህግ በክሱ ላይ አስፍሯል፡፡

No comments:

Post a Comment