Tuesday, February 9, 2016

የህወሀት የትግራይ ሪፐብሊክ ምስረታ የመጨረሻ ምእራፍ ላይ ደረሰ


አሁን የኢህአዴግ አገዛዝ በሀይልም ቢሆን ተገድዶ ሊወርድ እንደሚገባው መገንዘብ ካልቻልን ከገባንበት ረጀም ሰመመን ልጆቻችን ” በድሮው ጊዜ ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር ነበረች……” የሚል የታሪክ መጽሀፍ እያነበቡ እንነቃለን። ጀግናው የሀገሬ ህዝብ ሆይ እያንዳንዳችን በየአለን ሀቅም የምንችለውን ያህል የሀገራችንን ህልውና በማዳን ስራ ላይ እናውል ዘንድ በያለንበት እንድንደራጅ አስገዳጅ ጊዜ ላይ ደርሰናል!!!
በኢህአዴግ ላይ በህዝባዊ እምቢተኝነትም ሆነ በትጥቅ ትግል በተገኘው ሁሉ መንገድ አቅማችን በፈቀደልን ጉልበት፡ ህሊናችን በፈቀደልን ጥበበ ተጠቅመን፡ ፈጣሪን ደጀን አድርገን ልንነሳበት ጊዜው አሁን ነው። በጋንቤላ፡ በአማራ ክልል፡ በኦሮምያ፡ በደቡብ ኢትዮጵያ፡ በአፋር፡ በሶማሌ ክልል ባጠቃላይ በመላው የሀገራችን ክፍል ኢትዮጵያችን ከልክ በላይ እንደበሰለ ድንች በወያኔ ሴራ እየፈራረሰች፡ ከታላቅ ብሄራዊ ማንነት ወደ ትናናሽ ማንነቶች ድምርነት ተቀይራለች። ጥያቄ ያነሱ ዜጎች ካላንዳች ማቅማማት በወያኔ ስርአት ጠባቂወች የእስናይፐር ጥይት እየተመለሰላቸው እያየን ቆይተናል።
የህወሀት የትግራይ ሪፐብሊክ ምስረታ የመጨረሻ ምእራፍ ላይ እንደደረሰ ምልክቶች ሲታዩ ቆይተዋል። ከቀሪው የኢትዮጵያ ክፍል ቆርጦ የራስን ወሰን በማስፋትና ለወደፊትዋ ጎረቤት ሀገር ሱዳን በእጅ መንሻነት የወሰን ዳረጎት በማቅረብ ወደመጠናቀቁ ይገኛል። የመጭዋ ኢትዮጵያ ገጽታ ምን ሊመስል እንደሚችል እንኩዋን ለማሰብ እጅግ አስቸጋሪ ሆኖአለ። ያ ማለት እንደ ሀገር መቆየት ከቻለች ማለት ነው። የሰሜኑ ኢትዮጵያ ክልል “በትግራይ ሪፐብሊክ” ና በሱዳን ቅርምት ቅርጹን አጥቱዋል።
ይህንን እውን ለማድረግ አረመኔው ፋሽስት ወያኔ በአማራው ህዝብ ላይ ባዮሎጅካል መሳሪያ በመጠቀም የዘር ማጥፋት እርምጃ ከመውሰድ ባህል፡ ቁዋንቁዋና ማንነት በሀይል እስከማስቀየር የሚደርስ ናዚ በ ኦሽዌትዝ ካደረገው ግፍ የማይተናነስ ግፍ ፈጽሞአል።
በጥቂቱ ባለፉተ 3 ወራት ብቻ ዴሞክራሲያዊና ሰበዊ ጥያቄ በማንሳታቸው ምክንያት ብቻ ከ300 በላይ ዜጎች ተገድለዋል። እስረኛ እንደ ቦቆሎ በእሳት እየተለበለበ ሊያመልጥ የሞከረ በጥይት እንደቆሎ የተቆላውም በዚህ ሶስት ወር ውስጥ ነው።
በሰላማዊ ትግል በአንባገነኖች ጥላ ስር ሳይቀር የተደራጀንና ሀገራችንን ለማዳን የሞከርን ስንት ግፍ ተጎነጨን? ግን ወደ ቄራ እንደሚገባ በግ ሁላችንም ተራችንን እንጠብቃለን። በግፍ በምድር ካየኈቸው በሰብአዊነቱ አቻ ካላገኘሁለት አንዱ አለም አራጌ፡ ከቆፍጣናውና አንደበተ ርእቱ ብእረ ብርቱው በሀገር ፍቅር ልክፍት የናወዘው ጀግናው እስክንድር ነጋ ጀምሮ አእላፍ ወጣቶች ኣኣስርቤቶችን አጨናንቀዋል፡፡ ኢትዮጵያ የሚለው ስም የርሀብ እና የስደት ምሳሌ እደሆነ ቀጥሎአል። እንደ ጀግናዋ ወጣት ወይንሸት ስለሽ ያሉ ቆራጥ ቆፍጣና ሰላማዊ አርበኞች ዘር እንዳይተኩ ጽንስ የያዘ ማህጸናቸው በጭካኔ ባደባባይ ሲታሽ በድንዛዜ ተውጠን ተመለከትን።
ከብሉይ እስከ ሀዲስ በአለም ከተሰሙ ጭካኔዎች ይህች የኛዋ በመፍረስ ላይ ያለች ሀገር ያላስተናግደችው ምን አለ?
ዛሬ ከመቸውም በላይ አንድነት ያስፈልገናል። ከመቸውም በላይ በፍጹም ቁርጠኝነይ መደራጀትና መታገል ያስፈልገናል። ትግሉ በየ አንዳንዳችን በር አቅራቢያ እጁን ዘርግቶ በመጠባበቅ ላይ ይገኛል። ዙሪያችሁን ፈትሹ እርስ በእርሳችሁ እጅ ለእጅ ተያያዙ። በግንቦት ስላሴ እየተማማላችሁ አንድነታችሁን አጠንክሩ። እስላም ክርስትያኑ የብሔርን አሸንክታብ በጣጥሶ ጥሎ ከገባበት ድብርት ሊነቃቃ ይገባል። ልብ በሉ ጊዜ የለንም ሀገራችንን ወደመቀመቅ እየወረደች ነው። ጊዜ የለንም፡ ድንበራችንን ህጋዊ በሚሚስል ደባ የቴዎድሮስን እትብት ጨምሮ ይዞ በ30 ብር ተሽጥዋል። አሁን በቃ ካላልን ጊዜው መቸ ነው። በቃ እንበል። እኔ በበኩሌ ለወያኔ አገዛዝ እውቅና ከነሳሁ ቆየሁ፡፡ ኢትዮጵያ አሁን መንግስት የላትም!!! ህገመንግስትም የላትም!! ይህንን ያደረግሁት እኔ አይደለሁም፡ አምባገነኑ አገዛዝ እራሱ እንጅ።
የሰፊው ህዝብ ትግል ያቸንፋል!!!
ዳዊት አስራደ

No comments:

Post a Comment