Monday, February 1, 2016

በጋምቤላ የሚደርሰዉ የዘር ማጥፋት ስራ አሁንም አገርሽቶበታል::


የኢትዮጵያ ህዝብ ሰቀቀን እና ሰቆቃ ተቆጥሮ አላልቅ አለ:: በአኝዋክ ብሄር ላይ የደረሰዉ የዘር ማጥፋት ወንጀል የአለም አቀፉን ፍርድ ቤት ትኩረት ስቦ ሳይጨርስ በጋምቤላ የሚደርሰዉ የዘር ማጥፋት ስራ አሁንም አገርሽቶበታል::
ወያኔ የምትመራዉ መንግስት አለም አቀፍ ማህበረሰብ ቢጮሁበትም : ኢትዮጵያዉያን በጋራ ቢጮሁበትም : የጋምቤላ ማህበረሰብ በተናጠልም በጋራም ቢጮህበትም የጋምቤላ ህዝብ ላይ የሚያደርሰዉን ሰቆቃ ቀጥሎበታል:: ወያኔ ህዝቡን አንዴ ንዌር አንዴም አኝዋክ ሌላ ጊዜ አማራ እንዲሁም ኦሮሞ እያለ በጋምቤላ የሚኖረዉን ኢትዮጵያዉ እርስ በእርሱ ያጫርሰዋል::
የኢትዮጵያ ህዝብ ትሁትና ደግ ህዝብ ነዉ:: በጋምቤላ የሚኖረዉም እያንዳንዱ ማህበረሰብ ንዌርም ቢሆን አኝዋክም ቢሆን ትሁትና ደግ ህዝብ ነዉ:: ወያኔ ግን ማህበረሰቡን በጎሳ ከፋፍሎ ህዝቡን የማጫረስ የቤት ስራዉን የሚሰራዉ መልምሎ በሚያሰማራቸዉ የራሱ ካድሬዎች ነዉ:: ወያኔ ማንኛዉንም ማህበረሰብ ገብቶ ሲከፋፍል: ሲያጣላ እና እርስ በእርስ እንዲተላለቅ ሲያደርግ ሶስት ምክንያቶች አሉት:-
1. የተፈጠረበት የፍልስፍና አድማስ በጎሳ ፖለቲካ ማዕቀፍ ዉስጥ ስለሆነ ሁል ጊዜ ልዩነትን ጥላቻን እና መጠፋፋትን በማንኛዉም ህብረተሰብ ዉስጥ ሲገባ እንዲሰብክ አዉቆም ሳያዉቀዉም የራሱ ፍልስፍና ይጋብዘዋል
2. በማንኛዉም ማህበረሰብ ዉስጥ ህዝቡን እርስ በእርሱ ነጣጥሎ ካላቆመዉ ህዝቡ በጋራ ሊነሳብኝ ይችላል የሚል ስጋት አለዉ:: ስለዚህ አኝዋክንና ንዌርን መጀመሪያ በመነጣጣል አንዱን ብሄር የሱ ታማኝ አንደኛዉን ደግሞ ተሳዳጅ በማድረግ ስሌቱን ይቀምራል:: ሌላ ጊዜ አንድኛዉ አልታዘዝ ሲለዉ ደግሞ ስሌቱን ይገለብጠዋል:: አንዳንድ የዋህ ሰዉ ግን ወያኔ የንዌርን ብሄረሰብ የሚወድ ወይም የአኝዋክን ብሄረሰብ የሚጠላ ይመስለዋል:: እዉነታዉ ወያኔ ምንም የሚወደዉ ብሄረሰብ በኢትዮጵያ ሰማይ ስር የለም::
3. ማንኛዉንም የማህበረሰቡን ሀብት (መሬትና ልዩ ልዩ) ይዞታዎች ለመንጠቅ መጀመሪያ ህዝቡን እርስ በእርሱ ማጠፋፋት አለበት:: የጋምቤላን መሬት ለመንጠቅ እና ለሌባ ካድሬዎቹ: ለሌባ አለም አቀፍ ኢንቨስተር ተብዬዎች ለማስረከብ መጀመሪያ አኝዋኩን ማጥፋት ስለነበረበት የሰራዉን በደልና ክፋት ሁሉ ሰርቷል::አሁንም ይሄንኑ የማጠፋፋት ስራዉን ቀጥሎበታል::
እናም በሚያሳዝን ሁኔታ ይሄዉ የዘር ማጠፋፋት እና ጎሳን በጎሳ ላይ የማነሳሳት የቤት ስራዉን ቀጥሎበታል ብቻ ሳይሆን እንደ ትክክለኛ ስትራቴጅ እያከናወነዉ ነዉ::
የወያኔን ህሳቤ ማክሸፍ የሚቻለዉ አኝዋኮች ለብቻቸዉ ቆመዉ: ወይም አንዳንድ የወያኔ ጥቅም የገዛቸዉ የንዌር ማህበረሰብ ተወላጆች የሚሰሩትን ግፍ በማዬት ንዌሮች እንዲህ አደረጉ በማለት በጅምላ የንዌርን ማህበረሰብ በመክሰስ አይደለም::
የኢትዮጵያ ህዝብ በአጠቃላይ የወደፊት የእርስ በእርስ መጠላለፍና የጎሳ መርዛማ ጉድጓድ ዉስጥ እንዲገባ ወያኔ በሁሉም ህዝቦች መሃከል ልዩነት ዘርታ አሳድጋለች::ፍቅር ከመስበክ ጥላቻ መስበክ ቀላል ነዉ:: ጥላቻ በቀላሉ ብሶትን በመነካካት ሊራገብ ይቻላል:: እናም ወያኔ የዘራችዉ አስተሳሰብ ቀላል የሚመስለዉ ኢትዮጵያዊ መጀመሪያ ከንቅልፉ መንቃት መቻል አለበት::
ስለሆነም በአለ አዕምሮ የሆኑ ኢትዮጵያዉያን ነገሩን እንደገና ቆመዉ መመርመር አለባቸዉ:: የንዌር እና የአኝዋክ ምሁራን እና ባለ አዕምሮ ፖለቲከኞች ቁጭ ብለዉ መምከር አለባቸዉ:: አእምሮ ያላቸዉ ኢትዮጵያዉያን የአኝዋክ እና የንዌር ምሁራንን ከሌሎች ኢትዮጵያዉያን ፖለቲከኞች ጋር በጋራ ቆመዉ ለታላቅ ሀገር እንዲሰሩ በጋራ ለማነጋገር ብሎም ኢትዮጵያ ከገባችበት የጎሳ መርዛማ አዙሪት ዉስጥ እንድትወጣ ስራ መስራት አለባቸዉ::
ሌላ ምርጫ የለም:: ወያኔ የዘራችዉ አስተሳሰብን ነዉ:: ኢትዮጵያዊዉ ማህበረሰብንም ፈጽሞ ሊያጠፋፋ የሚችል መርዛማ አስተሳሰብን ረጭታ ነዉ:: ኢትዮጵያዉያን ይሄን አስተሳሰብ እንደ ህዝብ ማሸነፍ እስክንችል መከራና ሰቆቃችን ማለቂያም የለዉ::
አሁን በድጋሜ የተከሰተዉ የጋምቤላ ህዝብ ሰቆቃ : የእርስ በእስርስ መጨራረስ እና መጠፋፋት አንተ አኘዋክ ነህ አንተ ንዌር ይሄ ምድር የኔ እንጅ ያንተ አይደለም የሚለዉ መርዘኛ አስተሳሰብ ህዝባችንን ከፈጽሞ ጥፋት ጠርዝ ላይ ሳያደርሰዉ ኢትዮጵያዉያን ለጋራ ምክር መፋጠን ይገባቸዋል:: ይሄ ችግር ሁሉንም የኢትዮጵያ ማህበረሰብ አጋጥሞታል:: ይሄ ችግር ተናጠላዊ በሆነ አስተሳሰብ አይፈታም:: ሁል አቀፍ መፍተሄ ይፈልጋል እንጅ::
ኢትዮጵያ ሆይ እንግዲህ እግዚአብሄር ይማርሽ !
ወደ ፈጽሞ ጥፋት ገብተሽ የጠላቶሽ መሳቂያ ከመሆን ያዉጣሽ !
የወዳጆችሽም የልብ ህመም ከመሆን ትድኝ ዘንድ የሚፈዉስ የጥበብ ህሳቤ ወደ ህዝብሽ ልቦና ሁሉ ይግባልሽ !

No comments:

Post a Comment