Wednesday, December 30, 2015

የዞን 9 ጦማርያን ላይ አቃቤ ህግ የጠየቀው ይግባኝ በጠቅላይ ፍ/ቤት ተቀባይነት በማግኘቱ ጦማሪያኑ ዛሬ ፍ/ቤት ይቀርባሉ




የከፍተኛው ፍ/ቤት የዛሬ 3 ወር ገደማ በነፃ ያሰናበታቸው የዞን 9 ጦማርያን ላይ አቃቤ ህግ የጠየቀው ይግባኝ በጠቅላይ ፍ/ቤት ተቀባይነት በማግኘቱ ጦማሪያኑ ለታህሣሥ 20 እንዲቀርቡ ቀጠሮ ሰጠ፡፡
የፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በጦማሪያኑ ላይ የሰጠውን ብይን በመቃወም አቃቤ ህግ ይግባኝ የጠየቀባቸው ሶሊያና ሽመልስ፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ አቤል ዋበላ፣ አጥናፉ በርሄና ክሱ ከሽብር ወደ ወንጀል የዞረለት በፍቃዱ ኃይሉ በተሰጣቸው ቀጠሮ መሰረት ከጠዋቱ 2፡30 ለቃል ክርክር ተዘጋጅተው እንዲቀርቡ ፍ/ቤቱ አዟል፡፡
የከፍተኛው ፍ/ቤት ጥቅምት 5 ቀን 2008 ዓ.ም ጦማርያኑ በአቃቤ ህግ የቀረበባቸውን ክስ መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ ማሰናበቱ የሚታወስ ሲሆነ አቃቤ ህግ በበኩሉ፤ ጥቅምት 8 ለጠቅላይ ፍ/ቤት ባለ 11 ገፅ የይግባኝ ማመልከቻ ማስገባቱ ይታወቃል፡፡
ለ17 ወራት በእስር ላይ የቆዩት ጦማርያኑ፤ ጥቅምት 8 ቀን 2008 ዓ.ም ከማረሚያ ቤት መውጣታቸው ይታወሳል።
ጦማርያኑ የተከሰሱት የፀረ ሽብር አዋጁን በመተላለፍ፣ የሽብር ድርጊት ለመፈፀም በማቀድ፣ በመዘጋጀትና የሽብር ተሳትፎ በማድረግ በአሸባሪነት ከተፈረጁ ድርጅቶች ጋር ተሳትፈዋል፤ ስልጠናም ወስደዋል በሚል እንደነበር ይታወሳል፡፡
በሌላ በኩል ጦማርያኑ ከእስር ከተለቀቁ በኋላ ወደ መደበኛ ስራቸው መመለስ ቢሞክሩም መ/ቤታቸው ፈቃደኛ እንዳልሆኑ ገልፀዋል፡፡ በኢትዮጵያ አየር መንገድ ውስጥ በኬሚካል ኢንጅነርነት ተቀጥሮ ይሰራ የነበረው አቤል ዋበላ ለፍ/ቤቱ ባቀረበው አቤቱታ ወደ ስራ ገበታው ለመመለስ ቢፈልግም አየር መንገዱ ፍቃደኛ ሊሆን አልቻለም፡፡
ፍ/ቤቱም አየር መንገዱ ታህሣሥ 22 ቀርቦ ምላሽ እንዲሰጥ አዟል፡፡

No comments:

Post a Comment