Friday, September 2, 2016

አገሯን በመዉደዷ የልጅ እናት ታሰረች # ግርማ_ካሳ


አንዱዋለም አራጌ የሚባለውን ስም እናውቀዋለን ? ሃብታሙ አያሌው የሚባለውን ስም እናውቀዋለን ? ናትናዔል መኮንን፣ አንድዋለም አያሌው፣ ዳንኤል ሺበሺን ፣ ስንታየሁ ቸኮል፣ ዘሪሁን ገሰሰ፣ አንጋው ተገኝ፣ አባይ ዘዉዱ መሳይ መትኩ፣ ምርቱ ጉታ የተባሉትን ስሞች እናውቃቸዋለን ? የአንድ ወንድ ልጅ እናት የሆነችዉን የጎንደር ጀግና ሴት አስቴር ስዩምን እናውቃታለን ?
እነዚህና ሌሎች በመቶዎች የሚቆጠሩ በአንድነት ፓርቲ ዉስጥ በመታቀፍ ለአገርና ለሕዝብ ሲሉ ዋጋ የከፈሉና እየከፈሉ ያሉ በየቦታው በየወህኒ ቤቶች ይገኛሉ። የአንድነት ፓርቲ በሕወሃት የፖለቲክ ዉሳኔ የምርጫ ቦርድ ሰርተፊኬቱን ቢነጠቅም፣ አባላቱና መዋቅሩ ግን አሁንም አለ። አንድነት ፓርቲ አሁንም አለ። አባላቱ አሁንም ባገኙት አጋጣሚዎች ሁሉ የሕዝብን ብሶት እያጋለጡ ይሄንን ጨካኝ አገዛዝ እየታገሉት ነው። እስር ፣ እንግልት እንደሚመጣም እያወቁ፣ ሳይፈሩ፣ ሳይሸማቀቁ ነው ድምጻቸውን የሚያሰሙት።
ላለፉት በርካታ አመታት እየታሰሩ፣ እየተገደሉ ለአገርና ለሕዝብ ለቆሞ ወገኖቼ አክብሮቴ በጣም በጣም ትልቅ ነው። እያወሩ ብቻ ሳይሆን እየሰሩ ትግል ምን ማለት እንደሆነ ያሳዩን የለዉጥ ሃይሎች ናቸው።
ዛሬ ደግሞ እህት ወይንሸትን ስለሺን( winahabeshawit) ወስደዋታል። ወይንሸት የአንድነት ፓርቲ ብሄራዊ ምክር ቤት አባል እና የሴቶች ጉዳይ ም/ሃላፊ ነበረች። ነፍሰ ጡር የነበረች ጊዜ ደህንነቶች ሆዷን በመርገጥ ባደረሱባት ድብደባ ለከፍተኛ ሕመም ተዳርጋ ለብዙ ጊዜ በሆስፒታል እንድትተኛ ተደርጓል። በሐኪሞች ከፍተኛ ጥረት እና በመድሃኔ ዓለም ቸርነት ሕይወቷ ተርፎ አንዲት ቆንጅዬ ሴት ልጅም በሰላም ተገላግላለ። የወይንሸት ባለቤት፣ የልጇ አባት ፣ እርሱም በአንድነት ፓርቲ ዉስጥ ትልቅ አስተውጾ ሲያደርግ የነበረ አንጋፋ ታጋይ ሲሆን፣ የእስር ማዘዣ እንደወጣበት ሲረጋገጥ ወደ ጎሮቤት አገር ለጊዜው ፈቀቅ ማለትን መርጦ በዚያ ትግሉን እየቀጠለ ነው። ሕጻን ልጅ እናቷን በእሥር፣ አባቷን በስደት አጣች ማለት ነው።
እነርሱ ማስፈራራት ልማዳቸው ነው። ግን ወይንሸትን አላወቋትም። አንድነትን ስትቀላቀል፣ ትግሉን ስትቀላቀል፣ ዋጋ እንደሚያስፈለግ ጠንቅቃ ታውቃለች። ከአላማዋም ከግቧም ወደ ኋላ ዝንፍ የማትል ጀግና እህታችን ናት።
ወያኔዎች እየጨለመባቸው ነው። ወይንሸትን ጨመሮ የታሰሩ እስረኞች በሙሉ በቅርብ ይፈታሉ።
ከዚህ በታች ካሉት ፎቶዎች መካከል ወይንሸት በሰላማዊ ሰልፍ፣ አዎን በባህር ዳር ከተማ፣ “ከባዶ ጭንቅላት ባዶ እግር ይሻላል” የሚል መፈክር ይዛ፣ ተቃዉሞን ስታሰማና ሰልፈኛውን ስትመራ የሚያሳይ ሲሆን ሌላው ደግሞ በደህንነቶች ተደብድባ ሃኪም ተኝታ የሚያሳይ ነው፡፡
የሕወሃት ደህንነቶች እህቶች፣ እናቶች፣ ልጆች ላይ ሳይቀር እንደ አውሬ መጨቀኝ የለመደባቸው ናቸው። ብርቱክን ሚደቃሳ፣ ርዮት አለሙ፣ ማህሌት ፋንቱን፣ ኤዶም ካሳዬ …ይመስክሩ።
 

No comments:

Post a Comment