Thursday, February 26, 2015

የፊታችን አርብ ታላቅ አገር አቀፍ ተቃውሞ ይኖረናል «እስር ከትግላችን አያስቆመንም!» ድምጻችን ይሰማ!!


መንግስት ህገ መንግስታዊ መብቶቻችንን በመጣስ ላለፉት ሶስት ዓመታት ከፍተኛ በደል ሲፈጽምብን ቆይቷል። እኛም እንደህዝብ ድምጻችንን አዋህደን እና በአንድነት ቆመን ሰላማዊ ትግል ስናካሂድ ቆይተናል። ትግላችን እስካሁን አንድም ከሰላማዊነት መርህ ዝንፍ ሳይል የቀጠለ ሲሆን መንግስት ትግሉን ለማስቆም የሚወስዳቸው ግልብ እና አገር አጥፊ እርምጃዎችም ከመርሃችን ሊያዛንፉን እንደማይችሉ በተደጋጋሚ በተግባር ለማረጋገጥ ችለናል።
ሰሞኑን መንግስት በተለመደው ግፍ መር እርምጃው በርካታ ሙስሊም ወንድምና እህቶችን በማሰር ዘመቻ ላይ ተጠምዷል። አንዳችም ጥፋት ያልፈጸሙ ወጣቶችንም የ28 ቀን የፍርድ ቤት ቀጠሮ በመጠየቅ ወደማጎሪያ ካምፖቹ አስገብቷል። ይህ «ሙስሊሞችን በማሰር ከትግላቸው አስቆማለሁ!» ከሚል መናኛ ቀቢጸ ተስፋ እና ባዶ ምኞት የመነጨ ለመሆኑ እማኝ መጥራት አያሻም – ካሁን ቀደምም መንግስት ሲፈጽመው የቆየው፣ ግና ሊያሳካቸው ያልቻለው ህልሙ ነውና!
አዎን! ደጋግመን ስናሳይ እንደቆየነው ሁሉ ህዝብን ማንገላታት አንጂ ማሸነፍ ፈጽሞ የሚቻል አይደለም! ህዝብ ምንጊዜም አሸናፊ ነው! በአላህ ፈቃድ ያሸንፋልም! ይህን ህገወጥ እና ሊሳካ የማይችል እኩይ የመንግስት ምኞት በተለያዩ ስልቶች መታገል የነፍስ ወከፍ ሐላፊነታችን የሚሆነውም ለዚሁ እንጂ ለሌላ አይደለም። በመሆኑም ከነገ ወዲያ አርብ የካቲት 20/2007 መላው አገሪቱን ያሳተፈ ታላቅ አገር አቀፍ ተቃውሞ ይኖረናል። የተቃውሞውን መርሃ ግብር አስመልክቶ በነገው እለት የምናሳውቅ በመሆኑ እስከዚያው መረጃውን ላልደረሳቸው ሁሉ በማዳረስ ተዘጋጅተን እንጠብቅ፤ ድልም ከአላህ እንጂ ከሌላ አይደለምና!
ትግላችን እስከድል ደጃፎች በአላህ ፈቃድ ይቀጥላል!
ድምፃችን ይሰማ!

No comments:

Post a Comment